ዘረ ያዕቆብና ገብረ ህይወት ባይከዳኝ፤ ሁለት የዘመናዊነት እሳቤዎች በኢትዮጵያ ፍልስፍና፤ በፋሲል መርአዊ፤ (ሌክቸረር ፤ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፍልስፍና ት/ክፍል)
በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ የዘመናዊነት ሀሳብ ከአንድ ትውልድ ወደ ሌላ ትዉልድ፣ ከአንድ ዘመን ወደ ሌላው ዘመን እየተሸጋገረ ይሄዳል፡፡ ስለዚህም እያንዳንዱ ማህበረሰብ የበለጠ ዘመናዊና በለውጥ የሚያምን መሆኑን ለማሳየት ይሞክራል፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የዘመናዊነት ሀሳብ መገለጫዎች በተፈጥሮ የተለያዩ ናቸው፡፡ ስለዚህም በስነጥበብ፣ በፍልስፍና፣ በማህበረሰብ ትችና ዘመናዊ ትምህርት ውስጥ የተለያዩ ሀሳቦች ተንፀባርቀው እናገኛለን፡፡
በፍልስፍና መስክ ኢትዮጵያዊው ፈላስፋ ዘረያዕቆብ፣ የባህልና የወግ አስተሳሰቦችን ትችት በማዳበር በማህበረሰቡ ውስጥ ምክንያታዊነትና ማህበረሰባዊ ፍትህ እንዲሰፍን “ሐተታ” የተሰኘ ስራውን ለማዳበር ሞክሯል፤ ከዚህ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያዊው ምሁር ነጋድራስ ገብረህይወት ባይከዳኝ የሀገር በቀል ጥበብንና ምዕራባዊ ስልጣኔን ያጣመረ የዕድገት ጐዳና ለመቀየስ ሲሞክር ነበር፡፡ በነዚህ ሙከራዎች ላይ ተመርኩዘን ዘመናዊነት የበለጠ በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲዳብር ምክንያታዊ የሆነ ማህበረሰብ እንድያብብ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡