ስለ ባህል አንዳንድ ነጥቦች – የመነሻ ሀሳብ

            

በአካሉ ወልደማርያም ባሌ (ግለ- ማስታወሻ)     

ህዳር  2018

መንደርደሪያ፣

ኢትዮጵያ የብዝሀ  ብሄረሰቦችና ማህበረሰቦች ሀገር ናት፡፡ እነዚህ የኢትዮጵያ ብሄረሰቦችና ማህበረሰቦች አንደየአካባቢያቸው የተፈጥሮና የአየር ንብረት አንዲሁም በአንድ በኩል በተናጠል በሌላ በኩል ደግሞ እርስ በርስ ባደረጓቸው መስተጋብሮች  የፈጠሯቸው ብዝሀ ባህላዊ እሴቶች አሏቸው፡፡ እነዚህ ብዝሀ ባህላዊ እሴቶች ለፈጠሯቸው የህብረተሰብ ክፍሎች እየሰጡት ካሉ ፖለቲካዊ ፣ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጠቀሜታዎች በዘለለ በአገር አቀፍ ደረጃ አንድ የፖለቲካ እንዲሁም ተደጋጋፊ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ በመፍጠሩና ጠንካራ ሀገረ መንግስት በመገንባቱ  ረገድ የበኩላቸውን የማይታለፍ ድርሻ እንደሚወጡ ይታመናል፡፡

በዚህ ረገድ የሀገሪቱን ብዝሀ ባህሎች አስተባብሮ በመምራት ከዘርፉ የሚጠበቀውን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጠቀሜታ በአግባቡ ለማስመዝገብ እሴቶቹን በጥናት ላይ ተመስርቶ በማወቅ፤ በመረዳት፤ በመመዝገብና በማጥናት በአገር አቀፍም ሆነ በክልል ለሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች ምላሽ ለሀገር ልማትና እድገት ደግሞ መሰረት እንዲሆኑ ከማድረግ ባሻገር፤ አስተባብሮ በመምራት የሚገኘዉን ማህበረ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጠቀሜታ ለማረጋገጥ መስራት በየደረጃው ከሚገኙ የማህበረሰባችን ክፍሎች የላቀ ስራ ይጠበቃል፡፡

ስለሆነም፤ በዚህ የባህል አምድ ስር ስለ ባህል በአጠቃላይ፤ የባህል ምንነት ጠቀሜታና አተገባበር ከኢትዮጵያ አጠቃላይ ብሄረሰቦችና ማህበረሰቦች እንዲሁም አለም አቀፍ ተሞክሮ አንጻር ሃሳቦችን እየሰደርን የምናቀርብ ይሆናል፡፡ ጽሁፉ ተከታታይነት ባለው መልክ የሚቀርብና ሁሎቹንም የባህል ዘውጎችና ዘርፎች የሚዳስስ ሲሆን፤ ለዛሬ የባህልን ትርጓሜ፤ አለም አቀፍና አገር አቀፍ አተያይ በማሳያነት በማቅረብ አሃዱ ብለናል።

ባህል፣

ባህል አንድ ህብረተሰብ ወይም ማህበራዊ ቡድን ከሌላው ተለይቶ የሚታወቅበትንና ማንነቱን ለመግለፅ የሚያገለግሉትን መንፈሳዊ፣ ቁሳዊ፣ ምሁራዊና ስሜታዊ ገፅታዎች ሁሉ የሚያጠቃልል ሰፊ ፅንሰ ሀሳብ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ባህል ስነጥበብንና ስነፅሁፍን ብቻ ሳይሆን የአኗኗር ዘይቤዎችን፣ የሰው ልጅ መሰረታዊ መብቶችን፣ የዕሴት ስርአቶችን፣ ልማዶችንና እምነቶችን ጭምር የሚያካትት መስክ ነው፡፡ የሰው ልጅ የራሱን ማንነት የሚገልፅበትን ችሎታ የሚያገኘው በባህል አማካኝነት ነው፡፡ በስነምግባር የታነፀ፣ ከሌሎች ፍጡራን የተለየ፣ የማስተዋል ችሎታ ያለው ሰብአዊ ፍጡር ለመሆን የሚያበቃው ባህል ነው፡፡ አንዱን እሴት ከሌላው ለመለየትና ለመምረጥ የሚያስችለውም ባህል ነው፡፡ የሰው ልጅ የራሱን ስሜት የሚገልፀው፣ እሱነቱን የሚገነዘበው፣ ሰብዕናው ፍፁም እንከን የለሽ አለመሆኑን የሚያስተውለው፣ የራሱን ግኝቶች ትክክለኛነት በመጠራጠር የሚጠይቀው፣ አዳዲስ ትርጉሞችን ፍለጋ ሳይታክት የሚባዝነውና ከስልጣኑ በላይ የሆኑ ጉድለቶችን ለማስተላለፍ የሚያስችሉትን ስራዎች የሚፈጥረው በባህል አማካኝነት ነው፡፡ (ዩኔስኮ እ.ኤ.አ 1982 ሜክሲኮ.)

የባህል ዓለም አቀፋዊ አተያይ

ቀደም ባሉት ጊዜያት ባህል ሊኖረው ከሚገባ የኢኮኖሚ ልማት፣ የፖለቲካና ማህበራዊ ፋይዳ አንጻር ሲመዘን የነበረው ትኩረት አናሳ እንደነበር የተለያዩ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ሁኔታ እ.ኤ.አ. ከ1982 ወዲህ ለውጥ እያሳየ መጥቷል፡፡ በተለይም ደግሞ ዛሬ ባለንበት ዓለም ውስጥ ባህል ከኢኮኖሚ፣ ከማህበራዊ እንዲሁም ከተፈጥሮ አካባቢ የዕድገት መመዘኛዎች በተጨማሪ አራተኛ የዕድገት አምድ ወይም ምሰሶ መሆኑን የአለም አቀፉ ማህበረሰብም ሆነ መንግስታት ተቀብለውታል፡፡ ለዚህም እውን መሆን በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ቁም ነገሮች ውስጥ የባህል ለግጭት አፈታትና ለሰላም ግንባታ፣ለፈጠራ ስራ፣ ለማህበራዊ ትስስር፣ለተፈጥሮና አካባቢ ጥበቃ፣ የባህል ምርቶችና አገልግሎቶችን ለገበያ አቅርቦት በማዋል ለሀገር ብሄራዊ ገቢ ከሚኖረው አዎንታዊ አስተዋዕኦ እንዲሁም በሁለንተናዊው የልማት እንቅስቃሴ ውስጥ የበኩሉን ድርሻ ማበርከት ብቻ ሳይሆን በራሱ መቆም የሚችል የልማት ሃይል ሆኖ መገኘቱ፤ የሚሉት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

እነዚህንና ከላይ የጠቀስናቸውን ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ፋይዳዎች በተለያዩ አባል አገራት ተፈጻሚ ማድረግ ያስችሉ ዘንድ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽኖች ወጥተው ሀገራት እንዲቀበሏቸውና እንዲተግብሯቸው መደረጉ፣ የባህልንና የልማትን ጽኑ ቁርኝት በመገንዘብ በተለይም እ.ኤ.አ በ1992 በሴኔጋል ዋና ከተማ ዳካር እንዲሁም  እ.ኤ.አ በ 2ዐዐ5 ኬንያ ናይሮቢ ውስጥ ባህላዊ ኢንዱስትሪዎችን በአፍሪካ ውስጥ ለማሳደግና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎአቸውንም ለማጎልበት የተደረጉት ውይይቶች፤እ.ኤ.አ በ2002 ደቡብ አፍሪካ ውስጥ በተደረገው አለም አቀፍ ጉባኤ ላይ “ባህል የልማት አራተኛ አምድ” በሚል ያወጣውን የጁሀንስበርግ ዓለም አቀፍ ዲክላሬሽን ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት 64ኛው ጉባኤ ቀርቦና ድርጅቱም ውይይት አድርጎበት በ65ኛው ጉባኤ ተቀብሎና በ66ኛው ጉባኤ ደግሞ በዓለም አገራት ውስጥ የሚገኙ የተባባሩት መንግስታት ሁሎቹም ኤጀንሲዎች የልማት ዕቅዶቻቸው አካል በማድረግ እንዲስፈጽሟቸው መወሰኑ፤ እንዲሁም ከዚህ ቀደም ይታወቁ ከነበሩት የልማት አምዶች ማለትም ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና አካባቢ ጥበቃ በተጨማሪ ባህል የሚሊኒየሙ የልማት ግብ ፕሮግራም አካል እንዲሆን ማድረጋቸው ባህል ለእድገት ያለውን ወሳኝ ሚና ያመለክታል፡፡

በቀጣይም የባህልን ዘርፈ ብዙ አቅም ከተለያዩ የአለማችን አገራት አንጻር በመረጃ አስደግፈን  በተከታታይ የምናቀርብ ይሆናል።

የባህል አገራዊ አተያይ

ከላይ በመግቢው ውስጥ ለማመላከት እንደተሞከረው ሁሉ ኢትዮጵያ የብዝሀ-ብሄረሰቦችና ማህበረሰቦች አገር፣ በቁጥር በርካታ የሆኑ ብዝሀ- ባህላዊ እሴቶች፣ ምርቶችና መገልገያዎች እንዲሁም በዘመናዊው የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ አደረጃጀቶች ውስጥ ጉልህ ሚና ሊጫወቱ የሚችሉ ባህሎች ባለቤት ናት፡፡ እነዚህን ባህላዊ ክንዋኔዎችና እሴቶች አስተባብሮ በመምራት ለአገር እድገትና ልማት የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ለማድረግ የተሞከሩ ተግባራትን ስንመለከት በሙከራ ደረጃ ካልሆነ በስተቀር ውጤታቸው በግልጽ ታይቶና በሀገሪቱ ብሄራዊ ገቢ በቁጥር ሊገለጽ የሚችል ትርጉም ያለው ድርሻ ነበረው በማለት ደፍሮ መናገር የሚያስችል አልነበረም፡፡

በተለይም ባህልን ከኋላ ቀርነት ጋር አያይዞ የማየቱ የተንሽዋረረ አመለካከት ብዙ ያስከፈለን ስለመሆኑ አጠያያቂ አይደለም። ይህ የተለመደ አመለካከት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ዘርፉ የተለያየ ቅርጽና አደረጃጀት በመያዝ ውስን ዓላማዎች ለማሳካት በሚል የተቋቋሙና እስከ ቅርብ ጊዜም በመንቀሳቀስ ላይ ያሉ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ማህበራት ወዘተ መኖራቸው ግን አይካድም፡፡ለዚህ በማሳያነት ለማቅረብ ያህልም በኢትዮጵያ የዘመናዊ ባህል ታሪክና የአመራር ሂደት ውስጥ ልዩ ልዩ የባህል ተቋማት እንዲመሰረቱ፣ እንዲደራጁና አቅጣጫ እንዲይዙ ከተደረጉት እንቅስቃሴዎች ውስጥ ቀዳሚው በ1967 ዓ.ም ዘርፉ የሚኒስቴር መ/ቤት ሆኖ እንዲቋቋም መደረጉ እንደ አንዱ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል፡፡

በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የባህል ጉዳይ ህገመንግሥታዊ እውቅና ማግኘቱ፣ አስፈጻሚ መስሪያ ቤቶች በፌዴራል እና በክልል መቋቋማቸው፣የዘርፉን አቅጣጫ ያመላከተ የኢፌዲሪ የባህል ፖሊሲ በ1990 ዓ.ም መውጣቱ፤ እንደ አብዛኛዎቹ የአፍሪካ ሀገራት ሁሉ በኢትዮጵያም ውስጥ የባህል ኢንዱስትሪ እንደ አጀንዳ መታየት መጀመሩና በተለይም በእደ ጥበብ ውጤቶች ላይ ያተኮሩ አንዳንድ አበረታች እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ ያሉ መሆናቸው፤ እንዲሁም የተለያዩ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽኖችን በመቀበል እና የሚሊኒየሙን የልማት ግብ ለማስፈጸም ባህል አይነተኛ ሚና እንዳለው ማመን መቻሉ እውነት ቢሆንም በዝርዝር እያጠኑ አስፈላጊ ለሆኑ አላማዎች የማዋሉ ጉዳይ ዛሬም ትኩረትን ይሻል።

በመሆኑም በዚህ የመነሻ ሃሳብ ላይ ተመርኩዘን የተለያዩ የባህል ዘርፎችን ከአገራችን አንጻር በመቃኘት በወደፊት ጉዞአችን የምናቀርብ መሆኑን እየገለጽን፤ በዘርፉ ጠቃሚ ሃሳቦች፤ የውይይት መነሻዎችና ተመክሮዎች እንዲሁም ብዝሀ ባህሎች በጥናት ላይ ተመስርተን የምናቀርብና ከአንባቢያን የምንቀበል መሆኑን በማስገንዘብ ጭምር ነው።

Leave a Reply

Scroll to Top

Discover more from ሰምና ወርቅ

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading