ፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ በአዲስ አበባ ከተማ በ 1935 ዓ.ፈ. ተወለደ። አባቱና እናቱ ከባርቤዶስ ደሴት ወደ ኢትዮጵያ በመጡበት ጊዜ እናቱ ሚኞን ኢኒስ ፎርድ ባቋቋሙት የልዕልት ዘነበወርቅ ትምህርት ቤት የመማር እድል አግኝቷል። ወደ ዩናይትድ ስቴትስ በመምጣት ባገሩ አየር ኃይል ሰልጥኖ የጦር ጀቶችን ያበር ነበር። ኋላም በኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት ትምህርት ቤት ተመርቋል። ዋሺንግተን ዲ.ሲ በሚገኘው ሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ እስከ 2006 ዓ.ፈ ሰርቶ ጡረታውን ካስከበረ በኋላ ኑሮውን በኢትዮጵያ ለማድረግ ተመለሰ።
በ1981ዓ.ፈ. ላይ ወደ ሰሜን አሜሪካ ስመጣ የልጅነት ጓደኛየ ፕሮፌሰር ኃይሌ ገሪማ ከሥራ ባልደረባውና አለቃው ከፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ ጋር አስተዋወቀኝ። በ1983 ዓ.ፈ. ላይ ሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በቤተመጻሕፍት ቤት ተቀጥሬ መሥራት ስጀምር ሶስታችንም በሳምንት አንድ ቀን በተለይ አርብ ከሰዓት በኋላ በሃዋርድ ካፌ እየተገናኘን ስለሃገር ጉዳይ እንጨዋወት ነበር። ይህ የውይይት ግንኙነታችን ለብዙ ዓመታት ተካሂዷል። በ1985 ዓ.ፈ እኔና ባለቤቴ ለመጋባት በዲ.ሲ ከፍተኛ ፍርድ ቤት (DC Superior Court) ስንፈራረም ምስክር ሆነው ከፈረሙት አንዱ ፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ ነበር። በ 1987 ዓ.ፈ ደግሞ ልጃችን ሲወለድ ፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ ክርስትና አባቱ ሆኗል።
በዚሁ በ 1987 ዓ.ፈ ሰምና ወርቅ የጥናትና የምርምር መጽሔትን ማቋቋም ባሰብኩበት ጊዜ ለውይይት ከመረጥኳቸው ምሁራን አንዱ ፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ ነበር። የመጽሔቱ የዲሬክተሮች ቦርድ እንዲቋቋም ሲወሰን አቢይ ፎርድ የመጀመሪያው ሊቀመንበር ሆኖ ተመርጦ ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት አገልግሏል። ኋላም ስለኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ በ1991 ዓ.ፈ መጽሐፍ ሳዘጋጅ የመጽሐፉን ይዘት የሚያጎላ መግቢያ ጽፎ አበርክቷል።
ሰምና ወርቅ የጥናትና የምርምር መጽሔትን በምናዘጋጅበት ጊዜ በሚከሰቱ አንዳንድ ቅራኔዎች ላይ ፕሮፌሰር አቢይ ፈጥኖ መፍትሔ የማግኘት ችሎታ ነበረው። በዚህ ችሎታው ይህ መጽሔት ባጭሩ እንዳይቀጭ እየተከላከለ ለአራት ዓመታት እንዲቀጥል አስችሎታል። አንዳንድ የሃሳብ እርዳታ ስፈልግ ከፕሮፌሰር አቢይ ጋር በቀጠሮ ተገናኝተን የጻፍኩትን ሃሳብ አንብቤለት የርሱን ሃሳብ እና ትችት ተቀብየ ጽሑፌን ወይም ርእሰ አንቀጾችን መጨረስ የአሰራር ዘዴየ ነበር። እርሱም ደስ እያለው ባልተረዳው ነጥብ ላይ ጥያቄ በማንሳት፣ የላሉ አገላለጾችን ጠንከር እንዲሉ፣ አለቅጥ የጠነከሩ ነጥቦችን እንዲለዝቡ፣ ባጠቃላይ ገንቢ የሆኑ ሃሳቦችን እያቀረበ የመጽሔቱን ግስጋሴ እና እድሜ እንዲቀጥል አስችሏል።
የመጽሔቱ ስራ እንደቆመ ፕሮፌሰር አቢይ ወደ ኢትዮጵያ በመሄድ ኑሮውን በዚያ አደረገ። ይህን ያደረገበትም ምክንያት የጡረታ ጊዜውን ተወልዶ ያደገባትን ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን በመርዳት እና በማገልገል ለማሳለፍ በመወሰኑ ነበር። ስለዚህም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ተቀጥሮ አዲስ የተግባቦትና የጋዜጠኝነት ከፍተኛ ትምህርት የሚሰጥበት እድል በመክፈት ረገድ ከመሳተፉም ሌላ የትምህርት ቤቱ የመጀመሪያ አስተዳዳሪ በመሆን አገልግሏል። ኋላም በዚሁ ዩኒቨርሲቲ ፊልምን በማምረት ረገድ የመጀምሪያውን የዲግሪ ፕሮግራም አስተዋውቆ አልፎ አልፎ ትምህርት በመስጠት እየተሳተፈ ቁጥራቸው ብዙ የሆነ ምሩቃንን አፍርቷል።
ከተከበሩት አባቱ ከቄስ (Rabbi) አርኖልድ ፎርድ እና ከክብርት እናቱ ከወይዘሮ ሚኞን ፎርድ በወረሰው ኪዳን መሠረት እነዚህንና ሌሎችንም አቢይ እውቀት ነክ ጉዳዮች በማበረታታት ወጣት ኢትዮጵያውያንን ሲረዳ ከቆየ በኋላ ባደረበት ህመም ምክንያት ግንቦት1 ቀን 2010 ዓ.ም (May 9፣ 2018) ከዚህ ዓለም ተለይቷል።
የፕሮፌሰር አብርሃም አቢይ ፎርድን ነፍስ ከጻድቃን ጋር በእግዚአብሔር መንግሥት እንዲደምርልን አምላካችንን እንለምነዋለን።
የሰምና ወርቅ የጥናትና የምርምር መጽሔት አዘጋጆች በሙሉ ለፕሮፌሰር አቢይ ፎርድ ቤተሰብ በተለይ ለልጁ ሚኒ አቢይ እና ለልጅ ልጁ ፋሲል መጽናናትን ይስጣችሁ እንላለን።
ፈንታሁን ጥሩነህ